ፋሲለደስ

ፋሲለደስ

Saturday, April 8, 2023

ፕሮፓጋንዳ እንዴት ይሰራል

ፕሮፖጋንዳ ከየትኛዉም ዘመናዊ የጦር መሳሪያ የበለጠ ሀይል ያለዉ እና አንድን ዒላማ ያደረገበትን የህብረተሰብ ክፍል ሊያከሽፍ እና መልሶ ለራሱ ዓላማ መጠቀሚያ ሊያደርግ የሚችል መሳሪያ ነዉ።   
ዉጤታማ ፕሮፖጋንዳ ማለት ይህ ዒላማ የተደረገበት የህብረተሰብ ክፍል የያዘዉ አቋም አሊያም እዉነት ነዉ ብሎ የተቀበለዉ ሀሳብ በፕሮፓጋንዲስቱ ጫና ያልመጣ መስሎ ሲሰማዉ እና እራሱ አንፃራዊ ሁኔታዎችን መርምሮ የደረሰበት መደምደሚያ እንደሆነ ሲገምት ነዉ።  
ይህን አይነት "ዉጤታማ" የፕሮፓጋንዳ ስትራቴጂ ለመተግበር ፕሮፓጋንዲስቱ በቅድሚ የዚህን ዒላማ ያደረገበትን የህብረተሰብ ክፍል ማንነት እና ምንነት ያጠናል፤ ደካማ እና ጠንካራ ጎኑን ይፈትሻል፤ የመረጃ ምንጬን፣ መረጃዉን የሚያገኝበትን መንገድ እና መረብ ይመረምራል።  
ከዚህ ጥናት በኃላ በምን መልክ ምን መረጃ እንዴት ማቅረብ እንዳለበት እና ለምን ዓላማ ይህ ሊሆን እንደሚችል ይለያል።  
በተለያየ መንገድ ማለትም በመጽሀፍ፣ በምርምር መልክ፣ በትምህርት፣ በመገናኛ ብዙሀን፣ እናም በግለሰብ ደረጃ ፕሮፖጋንዳ ሊዛመት ይችላል 
በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ ላይ የተቃጣዉ አሉታዊ የፕሮፓጋንዳ ዘመቻ ረቂቅነትም ከዚህ የቆዬ ጥናት የመነጨ ነዉ። 
የሚቀርብልህን መረጃ መጠየቅ ካልቻልክ፣ በጥቅሉ እዉነት ነዉ ብለህ ከተቀበልከዉ ተሸንፈሀል።  እርግጥ ነዉ ትምህርት በከፍተኛ ደረጃ ንግድ እየሆነ በመጣበት በአሁኑ ዘመን ለእንደኛ ላለ ተራ የህብረተሰብ ክፍል ሁሉንም ለመመርመር የሚያስችል ማስረጃ ለማግኘት እና ይህንንም መንገድ ለመከተል ጊዜም ገንዘብም ይጠይቃል።
ነገር ግን መሰረታዊ የመጠየቅ ክህሎት ካዳበርክ ጉዳዩን ከስረ መሰረቱ ባትደርስበትም እንኳ በጥርጣሬ እንድትመለከተዉ ይረድሀል። 
ለምሳሌ ያህል በኢትዮጵያ ጉዳይ አንድ ዉሱን የምታምነዉን አቋም በጥቅሉ እንዉሰድ፣ ይሄን አቋምህን እንዴት እና በምን መረጃ ላይ ተመስርተህ ልትደግፍ ቻልክ? ለዚህ አቋምህ እዉነት ያልካቸዉን የመረጃ ምንጮች ከየት እና በምን መንገድ አገኘህ? እነዚህ የመረጃ ምንጮችህ የኋላ ታሪክ ምንድን ነዉ? ይህ የያዝከዉ አቋምህ ከሌላዉ ኢትዬጵያዊነትን በተመለከተ ካለዉ መሰረታዊ አቋምህ በምን መልኩ ይቃረናል ወይንስ ይታረቃል? ይሄን ፕሮፖጋንዳ በግልጽም በሽፋንም የሚያቀብሉህ አካላት የወሰድከዉን አቋም ተከትለህ ምን እንድታደርግ ነዉ የሚፈልጉት ? ይሄን መጠየቅ እና መመርመር ከቻልክ አይንህ እየተገለጠ እና እየሆነ ያለዉን እየተረዳህ ትሄዳለህ። 
የሚባለዉ እና በመሬት ላይ ያለዉን ነገር አነፃጽሮ እየሆነ ያለዉን መለየቱ ላይ ነዉ ቁም ነገሩ። 
ሰላም አሰፍናለሁ ያለህ ሁሉ የሰላም ዘብ ላይሆን ይችላል፤ የዴሞክራሲ ማማ ነኝ የሚልህ ሀገር እና መንግስት ሁሉ የሚለዉ እና እየሆነ ያለዉ የተለያየ ነገር ሊሆን ይችላል፤ አንድነትህን ላስጠብቅልህ የሚልህ ሁሉ የበለጠ ሊበትንህ ይችላል። አሊያም ነጻነት አመጣልሀለሁ ወይንም አመጣሁልህ ያለህ ሁሉ በአንድም ሆነ በሌላ መልኩ የባርነት ቀንበር ሊያጠልቅልህ እያመቻቸህ ሊሆን ይችላል።  ነፍሱን ለመታደግ እርዳታ የሚያስፈልገዉ ህዝብ እና መንግስት የቁስ እና የገንዘብ እርዳታ ለጋሽ ነኝ እያለ ሀገርህን ሊዘርፍህ ሲዳዳ ካመንክዉ ችግር ነዉ። 
አንተ በትክክል ምንድን ነዉ የምትፈልገዉ? ይሄ ፍላጎትህ እንዴት እና ከየት መጣ?  ፍላጎትህ እና ተግባርህ እንዴት ይግባባል? ይሄን መርምር እንጂ ጠበቃህ ነኝ ያለህ ሁሉ ለክስ እያመቻቸህ እንዳይሆን ተጠንቀቅ። 
ፕሮፓጋንዳ ሁሉ መጥፎ አላማ አለዉ ሊባል ባይችልም እንዲህ ኢትዬጵያ ላይ እንደተቃጣዉ ያለ እንደ ምስጥ ውስጣችንን ሰርስሮ ለመጣል የደረሰ አደገኛ ነገር የለም።  
እጅግ አደገኛ የሚያደርገዉ ደግሞ በአጠቃላይ በህልዉናችን የመጣ እና ሳናዉቀዉ የዚኽዉ የህልዉናችን ማጥፊያ መሳሪያ እና ሰለባ መሆናችን ነዉ።  
የፕሮፖጋንዲስት አላማ አዉቀኽዉም ሆነ ሳታዉቅ እንድትከተለዉ እና ለፈለገዉ ግብ መሳካት መሳሪያ እንድትሆነዉ ማድረግ ነዉ።  ከዚያ በኋላ አንተ ላይ ስለሚፈጠር ተፅዕኖ ሀላፊነት አይወስድም። 
ይሄንን የቆዬ የፕሮፖጋንዳ ዘመቻ ለመቋቋም የግድ ተቋማዊ የሆነ የካዉንተር ፕሮፖጋንዳ እና ኢንዶክትሬኔሽን ማዕከል በግልጽም ሆነ በሽፋን ሀገሪቱ ማቋቋም ያስፈልጋታል። ምክንያቱም በግለሰብ ደረጃ ይሄን ሁሉ ከብረት የከበደ የፕሮፖጋንዳ ናዳ ተቋቁሞ እና ተከላክሎ መቆም አይቻልም።

የአሜሪካ ወዳጅም ጠላትም መሆን አደጋው ብዙ መሆኑን ያለፉት የቅርብ ጊዜ የበርካታ ሃገራት ታሪክ በግልፅ ያሳያል።

የቀዝቃዛው ጦርነት እጅግ በተጋጋለበት የ1960ዎቹ መጨረሻ እና የ1970ዎቹ ዓመታት ወቅት እጅግ አወዛጋቢ አና በአሜሪካ የዉጭ ጉዳይ ፖሊሲ ከባድ ተፅዕኖ ፈጣሪ የነበረዉ ሄነሪ ኪሲንጀር በፖለቲካ ልሂቃን ዘንድ በተደጋጋሚ የሚወሳለት አንድ ድንቅ እውነት ተናግሯል።
ይሄውም "የአሜሪካ ጠላት መሆን አደገኛ ሊሆን ይችላል፤ የአሜሪካ ወዳጅ መሆን ግን በርግጠኝነት አጥፊ (ገዳይ) ነው" የሚለው ንግግሩ ነዉ።
"To be an enemy of America can be dangerous, but to be a friend is fatal. Henry Kissinger
ሄነሪ ኪሲንጀር በ1970ዎቹ በተለያዩ የኤዢያ፣ የአፍሪካ እና የደቡብ አሜሪካ ሃገራት አሜሪካ ታካሂድ በነበረው ጣልቃ ገብነት፣ የኮንቨርት እና ኦቨርት ስራ፣ የመንግስት ግልበጣ እና በርካታ  ቀጥተኛ እና የእጅ አዙር ጦርነቶች ዋና አርቃቂ እና ተዋናይ ስለነበረ ይሄ ንግግሩ ትልቅ ግምት የሚሰጠው ነው።
የአሜሪካ ወዳጅም ጠላትም መሆን አደጋው ብዙ መሆኑን ያለፉት የቅርብ ጊዜ የበርካታ ሃገራት ታሪክ በግልፅ ያሳያል። 
ወዳጅም ጠላትም ሳይሆኑ ኒዉትራል አቋም ይዞ መቆየቱ ላይ ነዉ ትልቁ ጥበብ። ይሄም ቢሆን እንደየሃገራቱ ፍላጎት ብቻ ላይወሰን ይችላል።
አንድ ሃገር ከአሜሪካ ጋር ያላትን ግንኙነት ለመወሰን ካላት አቅም በበለጠ አሜሪካ ከሃገሯ ጋር ያላትን ግንኙነት ለመወሰን ያላት ፍላጎት የበለጠ ተፅዕኖ አለው ።
ግኑኝነቱ በወዳጅነትም ሆነ በጠላትነት ይህ ግንኙነት ይዞት የሚመጣውን መዘዝ የሚከፍለው ግን የዛች ሃገር ህዝብ እና መንግስት ነው።
እንደ ኢትዮጵያ አይነት ትንሽ እና ደካማ ሃገር አሜሪካን ከመሰለ ግዙፍ እና እጀ ረዥም ሃገር ጋር የሚኖራት/ያላት ግንኙነት እንደ አሜሪካ ፍላጎት እና ሃገሪቱ በምታስቀምጠው ህግ እና ደምብ  እንዲሁም ቅርፅ እና ማዕቀፍ መሆኑ እሙን ነው። 
አሜሪካ ካላት አለም ዓቀፍ ተፅኖ የመፍጠር አቅም፣ እጅግ የተጋነነ ሃብት እና ቴክኖሎጂ ምንጭነት እና ወታደራዊ አቅም አንፃር ከሃገሪቱ ጋር በአንድም ሆነ በሌላ መልኩ ግንኙነት ሳይፈጥሩ ተገልሎ መኖር ይከብዳል።
ነገር ግን የአንድን ሃገር ዉሰጣዊ ጉዳይ ባሻት መልኩ በዲፕሎማሲም ሆነ በሌላ መልኩ ጣልቃ እንድትገባ እና ዉሳኔ ሰጪ አካል እንድትሆን መፍቀድ ይሄን ከመሰለው ግንኙነት ሊገኝ ከታሰበዉ ጥቅም ይልቅ ጉዳቱ ያመዝናል።
የኢትዬጵያው ጠቅላይ ሚኒስትር  ዶ/ር አብይ አህመድ በአሜሪካ በጎ ፈቃድ ስልጣን ላይ የወጣ መሆኑ ግልፅ የወጣ ነገር ቢሆንም በዚህ ውለታ የአድር ባይነት ባህሪውን ማጠናከሩ ዞሮ ዞሮ ህዝብ እና ሃገር እየጎዳ መሆኑን እያየን ነው። 
በተቃርኖ ጎን የቆመው እና የመንግስቱ ተገዳዳሪ ህውሃትም የአሜሪካ ተልኮ አስፈፃሚ ሆኖ መቅረቡ ችግሩን የበለጠ አወሳስቦታል።
አሁን ያለዉ የአለም ፖለቲካ እየከረረ መምጣት እና የቀዝቃዛው ጦርነት እንደገና ማገርሸት ደግሞ የኢትዬጵያን መንግስት በግልፅ ወገን ለይቶ እንዲቆም የሚያስገድደው ጊዜ እየመጣ ይመስላል። 
አሁን ካለዉ የመንግስታችን ግንኙነት እና አካሄድ መንግስት አጣብቂኝ ውስጥ የገባ እና ሳይወድ ተገዶ የአሜሪካን ጎራ የመረጠ ይመስላል።
ይህ ደግሞ ሊጠጋግነው ጀማምሮት የነበረውን ከኤርትራ እና ሌሎች ጎረቤት ሃገራት ጋር የነበረውን ግንኙነት መልሶ ያደፈርሰዋል። 
በዚህም ምክንያት በኢትዮጵያ ምናልባትም የዕርስ በዕርስ ጦርነት በድርድርም ሆነ በአሜሪካ ተፅእኖ ሊቆም ቢችልም ሌላ እጅግ የከፋ እና አውዳሚ ጦርነት መቀስቀሱ የማይቀር ነው።
ይሄውም ከኤርትራ ወይንም ከሱዳን እና ግብፅ አሊያም ከሶስቱም ሃገራት ጋር ይሆኖል።
እንግዲህ መንግስት አስተዳደር ላይ ያለው አካል ከህዝብ እና መንግስት ጥቅም አንፃር አይቶ ከአሜሪካ ጋር የመሠረተውን ግንኙነት መፈተሽ ጊዜ ሊሰጠው የሚገባ ጉዳይ አይመስለኝም። ካልረፈደ!

በአሁኑ ወቅት ሁለት ዓለማችንን ሊያጠፉ የሚችሉ ስጋቶች (Existential threats)

ስመ ጥሩዉ ይሁዲ አሜሪካዊ የቋንቋ እና የፖለቲካል ፍልስፍና ሊቅ ኖም ቾምስኪ በአሁኑ ወቅት ሁለት ዓለማችንን ሊያጠፉ የሚችሉ ስጋቶች (Existential threats) እውን ወደ መሆን እየተቃረቡ እንደሆነ በተለያዩ ፅሁፎቹ እና በተለያዩ መገናኛ ብዙሃን በሚሰጣቸው ቃለ መጠይቆች ደጋግሞ አሳስቧል። 
ይሄውም አየር(የተፈጥሮ) ፀባይ ለውጥ እና የኒኩለር ጦርነት ናቸው። 
ቾምስኪ ሁለቱም ዓለማችንን ሊያጠፉ የሚችሉት እነዚህ ስጋቶች ተያያዥ እና መንስዔውም አንድ እንደሆነ ያትታል። 
መንስዔዉም የኒዮሊበራሊዝም ፖለቲካል ኢኮኖሚ ስርዓት መስፋፋት ይሄን ተከትሎ እየሰፈነ የመጣው የኢምፔሪያሊዝም የአስተዳደር ስርዓት እንደሆነ ያስረዳል።
ኒዬሊበራልዚም የፖለቲካል ኢኮኖሚ መሠረቱ "ነፃ ገበያ" መር የንግድ ስርዓት ሲሆን ይሄን ተመክቶ በዓለም ላይ ያለ ሀብትን እና የገንዘብ ተቋምን መቆጣጠር ነው።
እንደ ቾምስኪ ትንታኔ "ነፃ ገበያ" እንደ ስሙ መጀመሪያ "ነፃ" ሳይሆን በብዙ ሸር የታጀበ የመንግስትን እና የህዝብን ሀብት ወደ ግል ንብረትነት ለማዞር ያለመ እና የገንዘብ ተቋማትን ለመቆጣጠር ያለመ የፖለቲካል ኢኮኖሚ ስርዓት ነው። 
ይሄን ለማስፈፀም ደግሞ ሃያላን ሀገራት ባቋቋሙት እንደ የተባበሩት መንግስታት፣ የዓለም ባንክ፣ የዓለም ዓቀፍ የገንዘብ ተቋም፣ የዓለም ንግድ ድርጅት፣ የአውሮፖ ህብረት የመሳሰሉ ግዙፍ ድርጅቶች አጋፋሪነት ከተለያዩ ጠንካራ እና ደካማ ሀገሮች ዘንድ በሚገባ ውል የቁጥጥር መንገዱን ያሰፋል።
ደካማ ሀገራት ከእነዚህ ሃያላን ሃገራት ጋር በሚገቡት ውስብስብ ውል የሀገር ውስጥ ገበያቸውን እና የገንዘብ ተቋማቸውን ለሃያላን ሀገራት ግዙፍ ኩባንያዎች ክፍት እንዲያደርጉ ይገደዳሉ።
ከዚህም አልፎ ሀገራቸውን እና ህዝባቸውን ከችጋር እና ይሄን ተከትሎ ሊመጣ ከሚችል አለመረጋጋት ሊያድን የሚችል የኢኮኖሚ እና የፖለቲካ ፖሊሲ የማውጣት ነፃነታቸውን ያጣሉ። 
ይሄንን አስገዳጅ ዓለም ዓቀፍ ውል ተገን አድርገው የሚመጡ የሃያላን ሃገራት እጅግ ግዙፍ ኩባንያዎችም በቀላሉ ወደ ደካማ ሀገራት ስለሚገቡ እና ስር ስለሚሰዱ የሀገሪቱን ሀብት እና የገንዘብ ተቋም ሀገር ውስጥ ያሉ ጥቃቅን ታዳጊ ኩባንያዎችን በቀላሉ በማሸነፍ እና ከውድድር በማስወጣት ይቆጣጠሩታል።
የአንድን ደካማ ሀገር ሀብት እና የገንዘብ ተቋም ከተቆጣጠርክ ደግሞ የሀገሯን ፖለቲካ በተፈለገው የፖለቲካ ቅርፅ እና ማዕቀፍ ለማደራጀት ምቹ ይሆናል። 
ይሄም ኢምፔሪያሊዝም እንዲሰፍን የሚያደርግ እና የአንድን ሀገር ጥሬ ሀብት የበለጠ ለመበዝበዝ እና ሙሉ የሀገሪቱን ሀብት ለእነዚህ እጅግ ግዙፍ ዓለም አቀፍ ኩባንያዎች ማዳበሪያነት ለማዋል እንዲጠቀሙበት ያደርጋል። 
ይህ ዞሮ ዞሮ ለበለጠ የአካባቢ ብክለት እና የአየር(ተፈጥሮ) ፀባይ ለውጥ አደጋ እንዲሁም ድህነት እና ይሄን ተከትሎ ለሚመጣ አለመረጋጋት ስለሚዳርግ ሀገሪቷን እና ህዝቧን የበለጠ ያደቃታል።
በአንድ ሀገር በአየር(የተፈጥሮ) ፀባይ ለውጥ እና አለመረጋጋት ምክንያት የሚመጣ ድህነት ደግሞ ለበለጠ ቁጥጥር እና የሀብት ምዝበራ ስለሚዳርግ ውጤቱ በመጀመሪያ ደረጃ ችግሩ ወደ ተፈጠረበት ምክንያት ይመራናል።
የበለጠ የሀብት እና የገንዘብ ተቋማት ቁጥጥር እና ኢምፔሪያሊዝም መስፋፋት! 
ይሄን እጅግ የተወሳሰበ መሠሪ የዓለም ስርዓት የሚቃወሙ ሀገራት እና መንግስታትን ደግሞ ከላይ የጠቀስኳቸው ዓለም ዓቀፍ ተቋማት(ድርጅቶች) እርዳታ እና ብድር በመከልከል፣ ማዕቀብ በማድረግ፣ የሀገር ውስጥ ገበያን በማዛባት እና ከዚህም የባሰ ሴራ በመጎንጎን ወደ ተፈለገው የድህነት ቀለበት እንዲገቡ ያስገድዳሉ።
የሀገሩ ህዝብ እና መንግስት ከዚህም የበለጠ ጠንካራ ተቃውሞ እና አቋም የሚያራምድ ከሆነ ደግሞ ሀገሩን እና ህዝቡን የማዳከም ሴራው የበለጠ ግልፅ እየሆነ እና እያየለ ይሄዳል። 
ይሄም ማለት እርስ በእርስ በመከፋፈል እና በማተራመስ፣ የመንግስት ግልበጣ በማድረግ፣ አሊያም የእጅ አዙር ጦርነት በማድረግ እንዲሁም ከዚህም ሲከፋ ቀጥታ ጦር በማዝመት ሀገርህን እና ህዝብህን ሊበትኑት እና መልሶ እንዳይነሳ ሊያደርጉት ይችላሉ። 
ለዚህም ብዙ ርቀህ ሳትሄድ የእኛን ሀገር ኢትዬጵያን፣ ሊቢያን፣ ሶማሊያን፣ ሴሪያን፣ የመንን፣ ኢራቅን፣ ኮንጎን ሌሎች የመካከለኛው ምስራቅ ኤዢያን እና የደቡብ አሜሪካ ሀገራትን ታሪክ መመርመር ከበቂ በላይ ማስረጃ ነው።
ይሄን "በነፃ ገበያ" መር የንግድ ስርዓት መሠረት የሚስፋፋ ኒዬ ሊበራል ፖለቲካል ኢኮኖሚ ፍልስፍናን እና የኢምፔሪያሊዝም አስተዳደር ስርዓትን መስፋፋት በበቂ ሁኔታ የተገዳደሩ እና ሃያላን ምዕራብያዊያን ሀገራትን እየተቋቋሙ የመጡ እንደ ቻይና እና ራሺያ የመሳሰሉ ግዙፍ ሀገራት ከዚህ የድህነት ቀለበት ለመውጣት የሚያደርጉት መፍጨርጨር ደግሞ ሁለተኛውን እጅግ ከባድ ስጋት ደቅኗል። 
ሁለተኛው ከባድ ስጋት ደግሞ መጀመሪያ ላይ እንደገለፅኩት የኒኩለር ጦር መቀስቀስ ስጋት ሲሆን አሁን ሁለቱ የዓለም ክፍሎች የሚገኙበት እጅግ አደገኛ መፋጠጥ ስጋቱን ወደ እውነትነት እያቀረበው ነው።
ራሺያ በዩክሬይን የከፈተችው ጦርነት እንዲሁም ቻይና ከታይዋን ራስ ገዝ አስተዳደር ጋር በተያያዘ የደረሰችበት መካረር እና ከምራብያውያን ጋር ያላቸው መፋጠጥ በማንኛውም ደረጃ ሶስተኛውን የዓለም ጦርነት ሊያስነሳ እና የኒኩለር ጦርነቱን እውን ሊያደርግ የሚችል ነው።
በዚህ መሀል ትልቁ ጥያቄ ሃገርህን እና ህዝብህን እዴት ትታደጋለህ የሚለው ነው?! 
በርግጥ የአየር(የተፈጥሮ) ፀባይ ለውጥም ሆነ የኒኩለር ጦርነት ዜሮ ድምር ያለው መላ አለምን ሊያጠፋ የሚችል እና አንድ ሀገር እና ህዝብ ከሌላው ተነጥሎ ሊተርፍበት የማይችል ክስተት ቢሆንም እስከዚያው ወደ እዚህ አውዳሚ ጥፋት ሊመራ የሚችል መንገድን ተቋቁሞ መቆየት ማምሻም እድሜ ነው እንደሚባለው ብልህነት ነው።
ለዚህ ግን የህዝብ አንድነት እና ሠላም እጅግ እጅግ ወሳኝ ቁምነገር ሲሆን ይሄንን የሀገር አንድነት እና የህዝብ ሠላም ለማምጣት ግን ከሁሉም ወገን ቅንነት እና ታጋሽነት እንዲሁም ከግል እና የራስ ጥቅም አሻግሮ አስተዋይነት ይጠይቃል። 
በመጀመሪያ ግን ያለውን ስጋት ጠንቅቆ መረዳት እና ማስረዳት ተገቢ እና ቅድሚያ የሚሰጠው ጉዳይ ነው።
ካልሆነ እያየነው እንዳለው ዓለም በእነዚህ ሁለቱ የአየር(ተፈጥሮ) ፀባይ ለውጥ እና የኒኩለር ጦርነት ምክንያት ካላት የመጥፋት ስጋት ቀድመን እንዳንከስም እሰጋለሁ።

Thursday, January 5, 2012

ፖለቲካዊ ሙስና እና የምርመራ ጋዜጠኝነት


በዓለምዓቀፍ ደረጃ ያለውን የፀረ-ሙስና እንቅስቃሴ በመምራት ላይ የሚገኘው ትራንስፓረንሲ ኢንተርናሽናል የሙስና ዓይነቶችን ጥቃቅን ሙስና፣ ግዙፍ ሙስና እና ፖለቲካዊ ሙስና በሚል በሶስት ይከፍላቸዋል፡፡  

  
እንደ ትራንስፓረንሲ ኢንተርናሽናል ትርጉም አሰጣጥ ጥቃቅን ሙስና ማለት በህግ የተሰጠን ሃላፊነት በማንኛውም መንገድ ያለአግባብ መጠቀም ሲሆን መሰረታዊ ግልጋሎቶችን ለማግኘት ዜጎች ከተለያዩ በዝቅተኛ እና በመካከለኛ ደረጃ የሚገኙ የመንግስት ባለስልጣናት ጋር በሚያደርጉት ግንኙነት ሊፈጠር የሚችል አድሎአዊ አሰራርን ያጠቃልላል፡፡ 


በሌላ በኩል ደግሞ በከፍተኛ ደረጃ በሚገኙ የመንግስት አካላት የመንግስት ሃብትን ለመመዝበር በሚያመች መልኩ ፖሊሲዎችን እና ህጎችን ያለአግባብ ለመተርጎም ሲሞክሩ እና የመንግስትን መሰረታዊ አቋም እንዲፋለስ ሲያደርጉ ግዙፍ ሙስና እንደሚሆን ድርጅቱ ያስረዳል፡፡


ማንኛውም አይነት የፖለቲካ ዓላማን ለማራመድ በሚል በገንዘብ ወይንም በአይነት የሚፈጸም ሙስና ፖለቲካዊ ሙስና ሲሆን ፖለቲካዊ ሙስና የሚፈፀመው  ደግሞ ንድገር የፖለቲካናት ላይ በሚገኙና ገር ሀብት ስርጭት ወይም ታላላቅ ፖሊሲዎችና ህጎች ላይ ለመወሰን ሥልጣንና ኃላፊነት ባላቸው አካላት ነው፡፡


በዚህ የስልጣን ደረጃ የሚገኙ ግለሰቦች ወይንም አካላት ፖለቲካዊ ሙስና የሚፈጽሙት አንድም ሀብት ለማካበት ሲሆን አንድም ደግሞ የስልጣን ቆይታ ጊዜያቸውን ለማራዘም ሊሆን ይችላል ፡፡ ይህ ማለት ንድ በኩል ስልጣንን ተጠቅመው ያለአግባብ ሃብት ሲያከማቹ በሌላ መንገድ ደግሞ የህዝብንና የመንግስትን ገንዘብ በመጠቀም የተደላደለ የስልጣን ደረጃ ላይ ተቀምጦ ለመቆየት ያስችላቸዋል፡፡


ሆኖም ትራንስፓረንሲ ኢንተርናሽናልም ሆነ ሌሎች በጉዳዩ ዙሪያ የሚሰሩ አካላት በሙስና ዙሪያ የሚወጡ በርካታ ጽሁፎች የሚያተኩሩት ስልጣንን ተጠቅሞ ያለግባብ ሃብት ማከማቸት ላይ ሲሆን “ፖለቲካዊ ሙስና ስልጣንን ለማራዘም” የሚለው ጉዳይ ግን በደንብ ያልታየና ጠለቅ ያለ ጥናት የሚያስፈልገው ጉዳይ እንደሆነ ይስማማሉ፡፡


ፅሁፎች ሲባል በጥናት መልክ የተዘጋጁ፣ ለውይይት መነሻ የሚቀርቡ አሊያም በመገናኛ ብዙሃን የሚዘገቡትን የሚያካትት ሲሆን የዚህ ችግር በሃገራችንም ይስተዋላል፡፡  


በኢትዮጵያ የፀረ-ሙስና እንቅስቃሴ ጉልህ አስተዋፅኦ እያበረከተ የሚገኘው ትራንስፓረንሲ ኢትዮጵያ በቅርብ ጊዜ በአዲስ አበባ ከተለያዩ የሃገር ውስጥ መገናኛ ብዙሃን ጋዜጠኞች ጋር አድርጎት በነበረው ውይይት ፅሁፍ አቅራቢ የነበሩት እንግዳ የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሃን በሙስና ዙሪያ የሚሰሩት ዘገባ በአብዛኛው ሃላፊነትን ያለአግባብ በመጠቀም ሃብት ምዝበራ ላይ ያተኮረ ሲሆን ያለአግባብ ስልጣንን ለማራዘም የሚደረግ እንቅስቃሴ ግን ትኩረት የተሰጠው እንዳልሆነ ተችተዋል፡፡

በዚህ አስተያየት መሰረት ሁለት መላምቶችን ማስቀመጥ የሚቻል ሲሆን የመጀመሪያው ስልጣንን ያለአግባብ ለማራዘም መሞከር በመገናኛ ብዙሃን ዘንድ እንደ ፖሊካዊ ሙስና አለመታየቱ ነው፡፡ ሁለተኛው መላምት ደግሞ ፖለቲካዊ ሙስና መልካም አስተዳደር በማስፈን ሂደትም ሆነ በልማት ላይ ሊያሳድር የሚችለውን ከፍተኛ አሉታዊ ተጽዕኖ መገናኛ ብዙሃን ባለመረዳታቸው ምክንያት ሊሆን ይችላል፡፡

የህዝብ ሃብትን በመመዝበር የስልጣንድሜን ለማስረዘም የሚደረገው ጥረት ብዙውን ጊዜድሎን ወይንም ጥቅምን ያማከለ የፖለቲካ ስርዓት ይፈጥራል፡፡ ይህ የፖለቲካ ሙስና የፖለቲካ አመለካከትን ያማከለ የገንዘብ፣ ቃ፣ የጥቅማ ጥቅም፣ ድሎችና ገፈቶች ክፍፍልን ያካትታል ፡፡ ፖለቲካዊ ሙስና ባጠቃላይ በዋናነት ሊያስከትላቸው የሚችለው ጉዳቶች የተቋማት ወድቀት፣ ስልጣን በዘፈቀደ መንገድ መያዝ፣ ምባገነንነት ባህሪን መላበስና የዜጎች ነጻነት መገደብ ናቸው ፡፡

ፖለቲካዊ ሙስናን ቴክኒካዊ ወይንም ቢሮክራሲያዊ በሆነ መንገድ ብቻ ማስቆምሊያም መቀነስ እንደማይቻል ድረ-ገፅን መሰረት ያደረገው እና በጸረ-ሙስና እንቅስቃሴ ዙሪያ ለሚሰሩ ተቋማት እንደ መረጃ ማዕከል ሆኖ የሚያገለግለው u4 የተባለ ተቋም ይገልጻል፡፡ እንደ u4 መረጃ ፖለቲካዊ ሙስና ራሱንንደቻለንድ የገበያ ችግር ወይንም የተበላሸ ስተዳደር ሥርዓት ተደርጎ ሊታይምይችልም ፡፡

የፖለቲካዊ ሙስናን ለመዋጋት ባለድርሻዎች የራሳቸውን ውስን ሚና የሚጫወቱበትን መንገድ ማፈላለግ የሚያስችል የፖለቲካ ባህሪ ያለው መፍትሄ ያሻል ፡፡ የችግሩን ምንጭ ማድረቅ ማለትም ፖለቲከኞች በፖለቲካ ስርዓቱግባብ ባልሆነ መንገድ የግል ጥቅማቸውን ሊያስከብሩ የሚችሉበትን መንገድ ማጥበብ ብሎም ለፖለቲካ ሙስና ሊኖር የሚችለውን ፍላጎት መቀነስንዱማራጭ ሊሆን ይችላል ፡፡ዚህ ላይ ከባድ ፈተና ሊሆን የሚችለው ለህገወጥ ምዝበራ ክፍት የሆኑ ቀዳዳዎችንንዴት መድፈን ይቻላል የሚለውናንዴት ግልጽነትን፣ ተጠያቂነትንና የውስጥ ቁጥጥር ስርዓትን መፍጠር ይቻላል የሚሉት ናቸው፡፡

በዋናነት የህዝብን ጥቅም ማስከበር ስለሆነ ዓላማቸው መገናኛ ብዙሃን በተለይ በዚህ ረገድ ግልጽነትን እና ተጠያቂነትን ለማስፈን የራሳቸውን የጎላ አስተዋጽኦ ማበርከት የሚያስችል ሰፊ እና እምቅ ሃይል እንዳላቸው እሙን ነው፡፡

ነገርግን ይህም እንዳይሆን ፖለቲካዊ ሙሰኞች  የመገናኛ ብዙሃን ነጻነትን በመገደብ የራሳቸውን ደህንነት እና የስልጣን መደላደል ሊያመቻቹ የሚችሉ ሲሆን ካላቸው የመወሰን አቅም ከፍተኛነት አንጻር መገናኛ ብዙሃኑንም ሆነ ጋዜጠኞችን ሊገዳደሩ ይችላሉ፡፡

የምርመራ ጋዜጠኝነት እጅግ አስፈላጊ ሆኖ የሚታየው እዚህ ላይ ነው፡፡ የምርመራ ጋዜጠኝነት ከተለመደው የጋዜጠኝነት ሙያ የሚለየው እጅግ ስልታዊ በሆነ አካሄድ በሚዘገበው ጉዳይ ላይ ጥልቅ ምልከታ፣ ዳሰሳ እና ትንተና ስለሚጠይቅ ሲሆን ሙስናን ለመዋጋት ጉልህ አስተዋጽኦ ሊጫወት ይችላል፡፡ እንዲህ አይነቱ የጋዜጠኝነት ሙያ ብዙውን ጊዜ የሚያተኩረው በከፍተኛ ደረጃ የተሰሩ ሙስናዎችን እንዲሁም ትላልቅ ድርጅቶች የሰሯቸውን ከፍተኛ ጥፋቶች በጥልቀት መርምሮ ይፋ ማውጣት ላይ ነው፡፡ በዚህም ምክንያት በጣም የተወሳሰቡ እና የተደበቁ ሙስናዎችን የሚያጋልጥ ሲሆን በመጨረሻም ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናትን ለደረሰው ጥፋት ተጠያቂ ሊያደርግ ይችላል፡፡


ሆኖም የምርመራ ጋዜጠኝነት እና በዘርፉ የሚሰሩ ጋዜጠኞች በርካታ ችግሮች ያሉባቸው ሲሆን ችግሮቹ ህልውናቸውን እስከመፈታተን እና የስራቸውን ጥራት እስከማበላሸት የሚያደርሱ ናቸው፡፡ በምርመራ ጋዜጠኝነት ዙሪያ ያለው ዋነኛ አጠያያቂ ጉዳይ ስራውን ለሚያከናውኑ ጋዜጠኞች እና ጥቆማ አቅራቢዎች በቂ ከለላ ሊሰጥ የሚችል ህግ አለመኖር ወይንም ያለው ህግ እና ተፈጻሚነት  ደካማ መሆን ነው፡፡ ከዚህ ባለፈ የአቅም ውሱንነት፣ የፋይናንስ እጥረት እና መገናኛ ብዙሃኑ ውስጥ ሙስና መበራከት በሀገራችን እንዲያውም የለም የተባለውን የምርመራ ጋዜጠኝነት የበለጠ ድራሹ እንዲጠፋ እያደረገው ነው፡፡


በዚህም ምክንያት ፖለቲካዊ ሙስና መድሃኒት ያልተገኘለት ከባድ የሃገራችን ችግር ሆኖ እንዲቆይ ግድ የሚል ሲሆን የፖለቲካዊ ሙስና መጠንከር የምርመራ ጋዜጠኝነትን እንደሚያዳክመው ሁሉ የምርመራ ጋዜጠኝነት መጠንከር ደግሞ ፖለቲካዊ ሙስናን እንደሚያዳክመው ግን እሙን ነው፡፡

Monday, December 26, 2011

አዲስ አበባ እንዴት እና ወዴት?


አዲስ አበባ እያደገች ነው፡፡ በዚህ ነዋሪዎቿም፣ መሪዎቿም፣ ቀያሾቿም፣ አልሚዎቿም ይስማማሉ፡፡ እንዴት እና ወዴት የሚለው ግን ሁሉንም የሚያሟግት ጉዳይ ነው፡፡ ከተወሰነ ግዜ በፊት በአዲስ አበባ የከተማ ልማት እድገት ዙሪያ የቴሌቪዥን ፕሮግራም ለመስራት አቅጄ ከላይ የጠቀስኳቸውን አራት አካላት አነጋግሬ ነበር፡፡ እነዚህ አካላት የሚከተሉትን አስተያየቶች ሰጥተውኛል፡፡

ከባለሙያዎች አንጻር በርካታ ልምድ ያላቸውን አራት የሚሆኑ አርክቴክቶች ያናገርኩ ሲሆን ከሞላ ጎደል ተመሳሳይ እይታ ነው ያላቸው፡፡ የአዲስ አበባን በፍጥነት እያደገች መሆን ሁሉም አርክቴክቶች ይስማሙበታል ነገር ግን ትክክለኛውን የእድገት ጎዳና ስለመከተሏ ጥያቄ አላቸው፡፡

እንደባለሙያዎቹ እይታ በከተማዋ የሚሰሩ ህንፃዎች የጥራት ደረጃ አጠያያቂ ነው፡፡ አንድ ህንፃ ማሟላት ከሚገባው መሰረታዊ ጉዳዮች አንጻር ቢታይ እንኳ የጣሪያ ከፍታ ማነስ፣ የአደጋ ግዜ መውጫ አለመኖር፣ በቂ የመኪና ማቆሚያ አለመኖር የመሳሰሉት ችግሮች ጎልተው ይታያሉ፡፡ ባለሙያዎቹ እንደሚሉት አንድ ህንፃ በአንድ ቦታ ሲሰራ የአካባቢውን አቀማመጥ፣ ታሪክ፣ ባህል እና ነዋሪ ከግምት ውስጥ ባስገባ መልኩ ዲዛይኑ መሰራት ሲገባው ባብዛኛው በአዲስ አበባ የሚሰሩ ህንፃዎች ከሌላ ቦታ መጥተው የበቀሉ ባዕድ ነገሮች ነው የሚመስሉት፡፡ የሃገሪቱን እና አካባቢውን እሴት ባካተተ መልኩ እየተሰሩ አይደለም፡፡ ለዚህ ዋነኛው ችግር ደግሞ አብዛኞዎቹ ባለሙያዎች የህንጻ ዲዛይን ሲሰሩ ወሳኞቹ እነሱ ሳይሆኑ ደንበኞቻቸው ስለሆኑ ነው፡፡ በዚህም ምክንያት ዛሬ አዲስ አበባ ውስጥ የመስተዋት ህንጻ መሰራት በሌለበት ቦታ ላይ የመስታዋት ህንፃ፣ የመስተዋት ህንጻ መሰራት ባለበት ቦታ ላይ ደግሞ የብሎኬት ወይንም የሸክላ አሊያም በሌላ ጥሬ እቃ የተሰራ ህንጻ የምናገኘው፡፡ 

በአንድ አካባቢ የተሰሩ ህንጻዎችን ስንመለከት ደግሞ እርስ በእርስ የመናበብ ችግር ያለባቸው እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ በአንድ መስመር ላይ የሚሰሩ ህንጻዎችን ብናይ እንኳ አንዱ ህንጻ ወደ መንገድ ገባ ብሎ ሲሰራ ሌላው ከመንገድ ወጣ ብሎ፣ አንዱ በብሎኬት፣ አንዱ በመስተዋት፣ አንዱ በሸክላ፣ ሌላው በሴራሚክ በመሳሰሉት በተዘበራረቀ መልክ የተሰሩ ናቸው፡፡ ጎን ለጎን በቆሙ ህንጻዎች መካከል የአንዱ ህንጻ ከፍታ እጅግ ረዝሞ የሌላው ደግሞ እጅግ አጥሮ ያልተመጣጠነ የከፍታ ልዩነት የሚስተዋልባቸው ህንጻዎችንም በከተማችን በብዛት እንደሚስተዋሉ አርክቴክቶቹ ታዝበዋል፡፡ የጎንዮሽ ስፋታቸውም አንዱ እጅግ ቀጥኖ እና አንዱ ሰፍቶ ይስተዋላል፡፡ ከቀለም አንጻር ደግሞ ሁሉም የመሰለውን ቀለም የሚቀባበት ልምድ እንዳለ ይገልጻሉ፡፡ እንደ አርክቴክቶቹ እምነት በአንድ አካባቢ የሚሰሩ ህንጻዎች የአካባቢ ልማት ፕላንን ተከትለው መሰራት የሚገባቸው ሲሆን ይህን ፕላን ተከትለው የማይሰሩ ከሆነ ግን አሁን እንደሚስተዋለው የተዘበራረቀ እይታን ይፈጥራሉ፡፡

ህንጻ መሰራት ባለበት ቦታ ቪላ ቤት፣ ቪላ መሰራት በሚገባው ቦታ ህንጻ፣ መናፈሻ ሊሆን የሚገባው የገበያ ማዕከል ወይንም የህንፃ ቦታ የሆኑ አካባቢዎች በከተማዋ የሚደጋገሙ ናቸው፡፡ በተለይ የህዝብ መናፈሻ ወይንም አረንጓዴ ቦታ የአንድ ከተማ ሳንባ ተደርጎ የሚቆጠር ሲሆን በአዲስ አበባ የህዝብ መናፈሻ ወይንም አረንጓዴ ቦታ ችላ ተብሏል፡፡  

ባለሙያዎቹ አዲስ አበባ ምን ትመስላለች ለሚለው ጥያቄ ይህን ትመስላለች ለማለት አስቸጋሪ ነው ይላሉ፡፡ እንደባለሙያዎቹ ገለጻ አዲስ አበባ አምስት ስድስት አይነት መልክ ያላት ሲሆን ይህን አይነት የተዘበራረቀ መልክ ያለው ከተማ በሌሎች ሃገሮች አይስተዋልም፡፡ 

የከተማዋ እድገት የሚበረታታ ቢሆንም እያደገች ያለችበት መንገድ ግን ሊጤን ይገባል ይላሉ፡፡ እንደእነሱ ገለጻ በአሁኑ ወቅት ህንጻ እየተሰራ ያለው በአብዛኛው በእንጨት ተሰርተው የነበሩ ያረጁ እና የደከሙ ቤቶች እየፈረሱ ሲሆን ይህ የሚያስከፍለው ዋጋ አነስተኛ ነው ነገር ግን የህንጻ አሰራራችን እና የአከባቢ ልማት እድገቱ በዚህ መልክ ከቀጠለ ይህን ለማስተካከል ወደፊት ህንጻዎችን ማፍረስ ሊጠበቅብን ነው ይህ ደግሞ እጅግ ውድ ዋጋ ያስከፍለናል፡፡

ከዚህ በፊት የሃገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር በብሄራዊው የቴሌቪዥን ጣቢያ ሲናገሩ እንደሰማሁት ከተማዋ ብዙ አይነት መልክ እንዳላት እና የመንግስታቸው ጥረትም ቢያንስ ሁለት መልክ ያላት ከተማ ለማድረግ መጣር እንደሆነ ነው፡፡ ይህን የእርሳቸውን አስተያየት ከሰማሁ በፊትም ሆነ ከግዜያት በሗላ በከተማዋ የተለያዩ ለውጦች የተደረጉ ሲሆን በተለይ የመንገድ እና የኮንዶሚኒየም ስራ ትኩረት ተሰጥቶት ሲሰራ ቆይቷል፡፡ ከዚህ ባለፈ ደግሞ በተለያዩ የከተማዋ ዝቅተኛ መንደሮች እንዲፈርሱ እና ለባለሃብት እንዲሰጡ ወይንም ሌላ ልማት እንዲከናወንባቸው እየተደረገ ነው፡፡ ያነጋገርኳቸው የከተማ ልማት ባለስልጣናት ይህ እንቅስቃሴ መንግስት ለከተማዋ እድገት ትኩረት ሰጥቶ እሰራ መሆኑን ያሳያል ይላሉ፡፡  

በህንጻ ዲዛይን እና የአካባቢ ልማት እድገት ዙሪያ ባለሙያዎች ለሚያነሱት ጥያቄ ግን ለራሳቸው ለባለሙያዎቹ ነጻነት ለመስጠት እና ፈጠራን ለማበረታታት ስንል ያደረግነው ነው የሚሉት፡፡ ያም ሆኖ የከተማዋ እድገት የተዘበራረቀ ነው ለሚለው ለዘብ ያለ አቋም ያላቸው ሲሆን እንደ ባለስልጣናቱ እምነት ከተማዋ በትክክለኛ የእድገት ጎዳና ላይ ትገኛለች፡፡ በከተማዋ የሚስተዋሉ አንድ አንድ ችግሮች የባለሙያዎች እና ባለሃብቶች ችግሮች ናቸው ይላሉ፡፡ ለምሳሌ ያህል አንድ ባለሃብት ህንጻ ሲያሰራ አረንጓዴ ቦታ መተው ሲገባው ያለክፍት ቦታ ሙሉ ለሙሉ ህንጻ የሚያሰራ ከሆነ ችግሩ የባለሃብቱ ነው ይላሉ፡፡

አብዛኞቹ ባለሃብቶች ህንጻ ለመስራት ቦታ በሊዝ መግዛት የሚጠበቅባቸው ሲሆን የሊዝ ዋጋ ውድ መሆን በሚሰሩት ህንጻ የጥራት ደረጃ ላይ የራሱ አሉታዊ ተፅእኖ እንዳለው ገልጸዋል፡፡ በከፍተኛ ዋጋ በሊዝ መሬት ከገዙ የገዙትን መሬት ሙሉ ለሙሉ “በአግባቡ” ሊጠቀሙበት እንደሚፈልጉ እና መንግስት ለአረንጓዴም ሆነ ለመኪና ማቆሚያ በሚል ከሚሸጥላቸው ቦታ ላይ ከሊዝ ነጻ የሚሰጣቸው እንደሌለ ይገልጻሉ፡፡ ስለዚህም አርንጓዴ ቦታ መተው ውድ ዋጋ ያወጡለትን ቦታ እንደማባከን እንደሚቆጥሩት ነው የገለጹት፡፡

የባለሙያዎች የመወሰን አቅም ማነስ ከባለሃብቶች በሚመጣ ከፍተኛ ተፅዕኖ እንዳልሆነም አስተባብለዋል፡፡ በእርግጥ ውጭ ያዩትን ህንጻ ዲዛይን አይነት በአዲስ አበባ የመስራት ፍላጎት እንዳላቸው ቢገልጹም የበለጠ ትኩረት የሚሰጡት ግን የጥሬ እቃ በቅርብ እና በርካሽ መገኝት፣ የህንጻው በፍጥነት ማለቅ እና ቶሎ አገልግሎት ላይ መዋል የመሳሰሉት ጉዳዮች እንደሆነ አስረድተዋል፡፡ 

አንድ አንድ ባለሃብቶች የሚያሰሩትን ህንጻ ኮንትራክት ደረጃውን ላልጠበቀ ተቋራጭ መስጠት በህንጻዎች ዲዛይን እና ግንባታ ወቅት ለሚያጋጥሙ መሰረታዊ ችግሮች እንደምክንያት ጠቅሰዋል፡፡ የባለሃብቶቹ እርስ በእርስ አለመናበብም ሌላው ችግር መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ 

የከተማዋ ነዋሪዎች የአዲስ አበባን እድገት በበጎ አይን ቢመለከቱትም እድገቱ መሰረታዊ ችግሮቻቸውን ፍትሃዊ በሆነ መልኩ በሚፈታ መልክ አለመሆኑ ይበልጥ ያሳስባቸዋል፡፡ በመንግስት በኩል ነዋሪዎችን የቤት እጥረት ለመፍታት ከፍተኛ ጥረት እተደረገ መሆኑ ቢነገርም ከፍተኛ መኖሪያ ቤት እጥረት እንዳለ ይናገራሉ፡፡

ከዚህ ባለፈ ደግሞ በአሁኑ ወቅት ለልማት በሚል በርካታ መንደሮች እየፈረሱ ሲሆን እነዚህ መንደሮች ሲፈርሱ የነዋሪዎቹን ችግር ትኩረት ሰጥቶ ሊፈታ በሚችል መልኩ ቢሰራ መልካም ነው ይላሉ፡፡ ነዋሪዎቹ ከቤታቸው እንዲፈናቀሉ ሲደረግ በቂ ዋስትና አለማግኘት እንዲሁም የሚሰጣቸውን ምትክ ኮንዶሚኒየም ለመግዛት አቅም ማነስ፣ ሲኖሩበት ከነበረው ቦታ አንጻር ከሚያከናውኑት ማህበራዊ እና ምጣኔሃብታዊ እንቅስቃሴ ጋር እጅግ የማይጣጣም ቦታ መመደብ የመሳሰሉ ችግሮች ጎልተው እንደሚታዩም በምሬት ጭምር ገልፀውልኛል፡፡ 

ነዋሪዎቹ እና ባለሙያዎቹ በይበልጥ ትኩረት የሰጡበት ጉዳይ የከተማ ልማት እድገት መንገድ እና ህንጻ ግንባታ ላይ ብቻ ትኩረት ያደረገ ሳይሆን የነዋሪውን እና ሰራተኛውን ዘርፈብዙ እንቅስቃሴ በሚያሳልጥ መልኩ ሰው ተኮር የከተማ ልማት እድገት ቢሆን መልካም መሆኑን ነው፡፡